በበአሉ ግርማ
ከጎራው ዘልቄ እስኪ ልነጋገር
ካለሰው ቢወዱት ምንያደርጋል ሃገር?
የኔ ውብ ከተማ
ህንጻ መች ሆነና የድንጋይ ክምር
የኔ ውብ ከተማ
መንገድ መች ሆነና የድንጋይ አጥር
የኔ ውብ ከተማ የኔ ውብ አገር
የሰው ልጅ ልብ ነው
የሌለው ዳርቻ የሌለው ድንበር፡፡
ህንጻው ምን ቢረዝም ምን ቢጸዳ ቤቱ
መንገዱ ቢሰፋ ቢንጣለል አስፋልቱ
ሰው በሰው ካልሸተተ ምንድነው ውበቱ?
የሰውን ልብ ነው!
ምን ቢነድ ከተማው ተንቦግቡጎ ቢጦፍ
ቢሞላ መንገዱ በሺህ ብርሃን ኩሬ
በሺህ ብርሃን ጎርፍ
ምን ያደርጋል?
ምን ያሳያል?
ካለሰው ልብ ብርሃን
ያ ዘላለማዊ ነበልባል ያ ተስፋ ሻማ
ጨለማ ነው ሁሌም ጨላማ!
Leave a comment