ኩሩ ኢትዮጵያዊ ለመሆን አንድ ተጨማሪ ምክንያት -አድዋ ዜና መዋዕል

ኩሩ ኢትዮጵያዊ ለመሆን አንድ ተጨማሪ ምክንያትአድዋ ዜና መዋዕል

<<የዛሬ ሳምንት አድርገው!!  በዚህ ላንተ   የሚደነግጥ ሰው  የለም። ሂድ የፎከርክበትን አሁኑኑ አድርገው። እኛም የመጣውን እንመልሰዋለን። እግሩን ለጠጠር፣  ደረቱን ለጦር ሰጥቶ አገሩን የማያድን ሰው  የሌለ እንዳይመስልህ። ደሙን አፍስሶ ለአገር መሞት ጌጥ ነው እንጂ ሞት   አይባልም። አሁኑኑ ሂድ አይምሽብህ፣  የፈከርክበትን ባሻህ ጊዜ ታደርገዋለህ። እኝም እዚያ እንጠብቅሃለን። እኔ ሴት  ነኝ፣  ጦርነት አልወድም፣  ግን  እንዲህ ዓይነቱን ውል  ከመቀበል ጦርነት እመርጣለሁ>>  እቴጌ በኮንት አንቶኔሊ ንግግር ተናድው የተናገሩት


 

ይህ   ጽሑፍ የአድዋን ድል  117ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በ2005 በእደ ማርያም እጅጉ ረታ የተጻፈ ነው። TO READ IN PDF TO READ IN PDF

ኢትዮጵያ ጥንታውያን ከሚባሉት ሀገሮች አንዷ ስትሆን፣  ከአምስት ሺህ  ዓመት ያላነሰ ታሪክ   አላት። በእነዚህ ዘመናት፣  ቀደምት አባቶቻችን ሠርተው፣  ትተውልን ካለፉት ሥራዎች መካከል የአክሱም ሐውልት፣የላሊበላ ቤተ  መቅደስ ሕንፃዎች፣  የጎንደር ቤተ  መንግስቶች ለምስክርነት የሚጠቀሱ ናቸው። ባለፉት በእነዚህ ዘመናት ሀገራችን የእርስ  በርስ   ጦርነትና ከውጭ በመጡ ወራሪዎች፣  ብዙ  ቅርሶች ወድመዋል፣  የሰዎች ሕይወት ጠፍቷል። ከእዚህ ሁሉ  ፈተና በኋላ፣  በዐሥራ ስምንተኛውና ዐሥራ ዘጠነኛው ምዕት ዓመት፣  ሀገራችን ዘመነ መሳፍንት በመባል የሚታወቀው ጊዜ ውስጥ ገባች። ያ ወቅት ደግሞ አውሮጳውያን አፍሪቃን እንደ ቅርጫ ሥጋ  ለመከፋፋል ወስነው ዘመቻቸውን የጀመሩበት ወቅት ነበር።

በዚያ ወቅት፣  ይህች   በዘመነ መሳፍንት አገዛዝ ኀይሏ የተዳከመችውን ሀገር መልሶ አንድ ለማድረግ፣ የቋራው አንበሳ ካሣ ኀይሉ፣  በኋላ ዳግማዊ ዐጤ   ቴዎድሮስ ተብለው የነገሡት ተነሡ። ዐጤ ቴዎድሮስም  በእነዚህ መሳፍንት ላይ በመዝመት ድል   አድርገው፤  ሀገራችን ኢትዮጵያ ተመልሳ እንደ ቀድሞው አንድ እንድትሆን መንገዱን ከፈቱ። ባደረጉትም ዘመቻ፣  አንድም ቀን  ድል   ሆነው የማያውቁት ንጉሠ ነገሥት፣  ከአውሮጳውያኑ ጋር  በተፈጠረው ችግር፣  የእንግሊዝ ጦር እስረኞቹን ለማስፈታት በዘመተባቸው ጊዜ፣ እጃቸውን ለወራሪው ጦር መስጠትን እንደ ውርደት ቆጥረውት መቅደላ አፋፍ ላይ ሽጉጣቸውን ጠጥተው የክብር ሞትን ጽዋ   ተቀብለዋል።

ይሁን እንጂ፣  ዐጤ ቴዎድሮስ ከሞቱ በኋላ የተነሡት  ነገሥታት እሳቸው የጀመሩትን ዓላማ በመከተል ኢትዮጵያ ተመልሳ አንድ እንድትሆን አድርገዋል።  ከዐጤ ቴዎድሮስ ቀጥለው የነገሡት ዐጤ   ዮሐንስ 4ኛ  ሲሆኑ፣  በእሳቸው ዘመን የሸዋው ንጉሥ ምኒልክ እና የጎጃሙ  ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት ግዛቶቻቸውን እንደያዙ  የዐጤ ዮሐንስን የበላይነት አሜን ብለው ተቀብለው ዕውቅና ሰጥተዋል። ይሁን እንጂ  በየበኩላቸው በቀጥታ ከውጭ ሀገር መንግሥታት ጋር  ቀጥታ ግንኙነት ያደርጉ  እንደነበር የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ።

አውሮጳውያን የአፍሪቃን ምድር፣  እንደ ቅርጫ ሥጋ  በሚቀራመቱበት በዚያ ወቅት፣  ኢጣሊያ በበኩሏ፣   በባህረ ነጋሽ   በተባለው፣ እነርሱ ግን  በኋላ ኤርትራ የሚል ስም   የሰጧት፣  የቀይ ባሕር ጠረፍ ላይ   እግሯን ተክላ ነበር። እንደልቧ ለመስፋፋት ግን፣  ዐጤ   ዮሐንስ እንቅፋት ስለሆኑባት፣ የወሰደችው አማራጭ ከሌሎቹ ነገሥታት (ንጉሥ  ምኒልክ እና ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት)ጋር  ጥሩ የወዳጃነት ግንኙነት መፍጠር ነው። ይኽም ኢጣሊያ ወደፊት ዐፄ ዮሐንስ ላይ  ስትዘምት እንዲተባሩዋት  ለማድረግ በማሰብ ነበር።  ዋናው ሐሳብ ይህ   ሆኖ  ሳለ  ነገር ግን  በአሰብ ወደብ ስለሚገቡ ዕቃዎች ቀረጥና በሸዋ ስለሚኖሩ ኢጣሊያኖች ሁኔታ   ለመነጋገርና ፔትሮ አንቶኔሊ መልእክተኛ ሆኖ  ወደ ንጉሥ ምኒልክ በ21   ሜይ   1883 ዓመተ ምሕረት በመምጣት ውል  ተፈራረመ።  ንጉሥ ምኒልክም ወደፊት  በዐጤ ዮሐንስ ላይ   ለመዝመት እንዲያስችላቸው የጦር መሣሪያ እንዲገዙ ተስማሙ። ኢጣሊያኖችም በእውነት ንጉሥ ምኒልክ በዐፄ   ዮሐንስ ላይ  ይዘምታሉ ብለው ስላመኑ ተጨማሪ የጦር መሣሪያ በመስጠትና እንዲሁም ብዙ  ብድር በመፍቀድ የንጉሥ ምኒልክ ጦር ይበልጥ እንዲጠናከር አደረጉት። በዚህ መኸል፣  ዐጤ   ዮሐንስ፣  እንግሊዞች በስምምነታቸው መሠረት፣  ምፅዋን ለኢትዮጵያ በማስረከብ ፈንታ ለኢጣሊያ መስጠታቸውን ንጉሥ ምኒልክ እንዲያወቁ  አደረጉ።  ንጉሥ ምኒልክ አንቶኔሊን በአስቸኳይ ጠርተው፣  ሁኔታውን እንዲያስረዳ ለጠየቁት የሰጣቸው መልስ ስላላረካቸው፣ ከዚያን ጊItegue and Menelikዜ ጀምሮ በጣሊያኖች ላይ ጥርጣሬ አደረባቸው።             እቴጌ ጣይቱና ዳግማዊ አጤ ምንልክ

እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር (እ.አ.አ)ሚያዚያ  1889 ንጉሥ ምኒልክና እቴጌ  ጣይቱ ወሎ  ላይ ውጫሌ በሚባለው ቦታ  ሳሉ  እያሉ ዐጤ   ዮሐንስ መተማ ላይ   መሞታቸውን ሰሙ። በአጋጣሚ ሆኖ አንቶኔሊ ተጨማሪ የጦር መሣሪያ ይዞ ሲመጣ ንጉሥ ምኒልክ እንጦጦ ስላልነበሩ፣  ውጫሌ ሄዶ አገኛቸው። አንቶኔሊ ንጉሡ ወደ   መናገሻ ከተማቸው እስኪመለሱ ድረስ መታገስ አቅቶት ወደ   ውጫሌ የሄደው፣  በኢጣሊያኖች የተረቀቀውን ውል  ለማስፈረም ነበር። ሃያ አንቀጽ ያለውን ይኽን   ውል  ንጉሥ ምኒልክና እንዲሁም በንጉሥ ኡምቤርቶ ስም   አንቶኔሊ ሆኖ  ፈረሙ። ይህ     ውል፣  በተፈረመበትን ቦታ ስም   <<የውጫሌ ውል>>   ተባለ። ይሁን እንጂ፣  ከዚህ ውል  ውስጥ 17ኛው አንቀጽ አማርኛው፣ <<የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ከአውሮጳ ነገሥታት ለሚፈልጉት ጉዳይ ሁሉ  በኢጣሊያ መንግሥት አጋዥነት መላላክ ይቻላቸዋል>> ሲል፣  የኢጣሊያንኛው ደግሞ <<የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ከአውሮጳ ነገሥታት ለሚፈልጉት ግንኙነት በኢጣሊያ መንግሥት አማካይነት ማድረግ ይገባቸዋል>> ይላል። ይህ አንቀጽ ውሎ  አድሮ በሁለቱ ሀገሮች መካካል የአድዋ ጦርነት ተብሎ ለሚታወቀው መነሻ ምክኒያት ሆኗል።

የአድዋ ጦርነት

የኢትዮጵያ  ሠራዊት በአድዋ አካባቢ ከሰፈረበት ከፌብሩዋሪ 23   እስከ 28   ጀምሮ፣  ምሽጋቸውን አጠናክረው ሲሠሩ ለጦርነት ዝግጁ ሆኑ። ኢጣሊያኖችን ከምሽጋቸው እንዲወጡ ለማድረግም የፕሮፓጋንዳውን ሥራ  ተያያዙት። ይህንን ያደረጉት የኢትዮጵያ ሠራዊት ምግብና አንዳንድ ነገሮችን ፍለጋ ኢጣሊያኖቹ ወደ   አሉበት መንደር አካባቢ ሲሄዱ፤  የኢጣሊያኖቹ ሰላዮች በምስጢር ግን  የዐጤ ምኒልክ የሆኑት ለጣሊያኑ ጦር አዛዥ ለባራቴየሪ፤

  • ብዙ ወታደሮች ጦርነቱ ገና ብዙ  ጊዜ ይወስዳል እንዲሁም የጣሊያንን ትልልቅ መድፍ ለመቋቋም አንችልም ብለው ፈርተው እየከዱ  ወደመጡበት ሀገራቸው እየተመለሱ  ነው።

  • የጐጃሙ ንጉሥ ከዐጤ ምኒልክ ተቃቅረዋል ስለዚህ ጦራቸውን ይዘው ወደ ጐጃም ሊመለሱ ነው።

  • እንዲሁም ራስ መኮንን ለማመጽ እየተዘጋጁ ነው።

  • አብዛኛው ሠራዊት አክሱም ጽዮን ለመሳለም ሄዷል የሚል የፈጠራ ወሬ  ሪፖርት አቀረቡ።

በፌብሩዋሪ 28፤  ጄኔራል ባራቴየሪ፣ ሌሎቹን የጦር ሹማምንቶች ጄኔራሎች፣ አልቤርቶኒን፣ አሪሞንዲን፣  ዳቦርሚዳንና ኤሌናን ስብሰባ ጠራ። ጄኔራል ባራቴየሪም ያላቸው ስንቅ   ለ4   ቀን  ብቻ የሚበቃ መሆኑን ገልጾ፣  ያለውም አማራጭ ወደ   አስመራ ማፈግፈግ ወይም ደግሞ የኢትዮጵያን  ጦር ማጥቃት ነው  ሲል  ስብሰባውን ጀመረ።  አራቱም ጄኔራሎች ወደ   አስመራ ማፈግፈግ የሚለውን በአንድ ድምፅ ተቃውመው፣ በኢትዮጵያ ጦር ላይ   ዘምተው ጥቃት በመፈጸም፣  አምባላጌና መቀሌ ላይ  የደረሰባቸውን ውርደት ማስወገድ እንዳለባቸው በቁጭት ተናገሩ።  ጦርነቱም በማግሥቱ በፌብሩዋሪ 29 ሊያደርጉ ወሰኑ።

1456729973025በአድዋ የኢትዮጵያ  ሠራዊት አሰላለፍ እንደሚከተለው ታቀደ። ዐጤ ምኒልክ፣  በአባ ገሪማ ኮረብታ ከቤተ መንግሥቱ የጥበቃ ሠራዊት ጋር  ሲሰፍሩ፤  እቴጌ ጣይቱ ደግሞ እዚያው አጠገብ 5 ሺህ የሚሆን ጦራቸውን ከመድፋቸው ጋራ  ይዘው ሰፈሩ። ከእቴጌ ጋራ  ወ/ሮ  ዘውዲቱ ምንሊክና ሌሎች የቤተ መንግሥቱ ሴቶች ነበሩ። እነዚህ በጦርነቱ ሰዓት ውሃ፣  ጥይት በማቀበልና ቁስለኞችን በመንከባከብ የሚረዱ ነበር። በዚህ ጊዜ፣ ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት 12 ሺህ  ጦራቸውን ይዘው በመሄድ፣  በስተቀኝ በኩል   አጥቂ ሆነው   ተሰለፉ። ራስ  መንገሻና ራስ  አሉላ፣ 13  ሺህ  ጦራቸውን ይዘው ኪዳነ ምሕረት ላይ ሰፈሩ። የራስ መኮንን፣  የራስ ሚካኤል እና የራስ ወሌ  ጦር ደግሞ የመኻከሉን ቦታ  ያዘ።

የጦርነቱ ዋዜማ የካቲት ፳፪

3:00 (9:00 pm)       

ቅዳሜ ከምሽቱ ሦስት ሰዓት ላይ ጄኔራል ባራቲየሪ ጨለማን ተገን በማድረግ ቁጥሩ 17   ሺህ  (10,600  ኢጣሊያኖች እና 7000 ተወላጆችን)  የሆነውን አራት ብርጌድ ጦር ይዞ፣  አድዋ ላይ   የሰፈረውን የኢትዮጵያን ጦር ለመውጋት ጉዞ ጀመረ። የጉዞውም ዕቅድ፣  አራቱ ብርጌዶች በተለያየ አቅጣጫ ተጉዞው፣ እተመደበላቸው ቦታ  ላይ   ከመንጋቱ በፊት እንዲደርሱና፣  የኢትዮጵያን ጦር ከከፍታ ቦታ ላይ ሆነው ከበው እንዲያጠቁ ነበር። ይሁን እንጂ፣  በዚያ ጭለማ የያዙት ካርታ ትክክል ስላልነበር፣  በተጨማሪም ጦሩን የሚመሩት ኤርትራውያን በምሥጢር የሚሠሩት ለዐጤ ምኒልክ ስለነበር፣  ጉዞአቸው አስቸጋሪ ነበር።

8:30 (2:30 am)          

በጄኔራል   ባራቲየሪና በጄኔራል ጁሴፔ ኤሌና የሚመሩት ብርጌዶች በ8:30  ሰዓት ላይ እሻሾ ተራራ ደረሰ። ሁለቱ ብርጌዶች በታዘዙት መሠረት በጄኔራል   አልቤርቶኒ የሚመራው ጦር በስተግራ ታጥፎ፣  ወደ  ኪዳነ ምሕረት ሲሄድ፤  የጄኔራል ዳቦርሚዳ ብርጌድ ጦር በቀኝ  በኩል   አልፎ ከፍ  ያለውን ገዥ  መሬት (ኮረብታ) ለመያዝ ጉዞውን ሲቀጥል፣  ጄኔራል አሪሞንዲ መሐሉን ይዞ ተጓዘ።

10:00 (4:00 am) 

ጄኔራል አልቤርቶኒ እንደታዘዘው፣  ጦሩን እየመራ ኪዳነ ምሕረት ደረስኩ ብሎ ሲያስብ፣  አሳሳች መንገድ መሪዎቹ ኤርትራውያን (ለዐጤ  ምኒልክ በምስጢር የሚሠሩ)፣  ኪዳነ ምሕረት ገና አልደረስንም ገና ብዙ  መንገድ ይቀረናል በማለት ሌላ  4.5  ማይልስ ጉዞ ወደፊት   ቀጠሉ። 2.5  ማይልስ እንደተጓዙ፣  በራስ አሉላ ከሚመራው ጦር ጋር  ተገናኙ። እንግዲህ የመጀመሪያው  ተኩስ ልውውጥ በዚህ ቦታ  ላይ   ተጀመረ። ሌሎቹም ብርጌዶች በየታዘዙበት አቅጣጫ ቢጓዙም፣ በዚያ ባልለመዱት ምድር የተጓዙት ጊዜው ያለፈበት ካርታ በመጠቀማቸውና፣ የአሳሳች  መሪዎቻቸውን ኤርትራውያን ቃል  አምነው፣  እንደታሰበው ተቀራርበው ሳይሆን የሠፈሩት፤  በጣም ተራርቅው ነበር።

በዚያች ሌሊት፣  ኢጣሊያኖችቹ ወጣ  ገባውን መንገድ በድቅድቅ ጨለማ ሲጓዙ፣ ዐጤ ምኒልክ፣  እቴጌ ጣይቱ፣  ንጉሥ ተ/ሃይማኖት  እንዲሁም ሌሎች ራሶች፣ አድዋ  በሚገኘው በቅዱስ ሚካኤል ቤተ  ክርስቲያን ነበሩ። አንዳንድ ጸሐፊዎች፣ ዐጤ ምኒልክ በዚያች ሰዓት ቤተ ክርስቲያን  ሳይሆን በድንኳናቸው ውስጥ ነበሩ ብለው ጽፈዋል። የሆኖ ሆኖ  መልእክተኛ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥቶ ጠላት መምጣቱንና ጦርነት መጀመሩን ተናገረ።  አቡኑም ከቤተ መቅደሱ ወጥተው፣ <<ልጆቼ ሆይ፣ ዛሬ  የእግዚአብሔር ፍርድ የሚገለጥበት ቀን ነው። ሂዱ፣ ለሃይማኖታችሁና ለንጉሣችሁ ተዋጉ። ሁላችሁንም ከኃጢአታችሁ እግዚአብሔር ይፍታ>> ብለው አሳረጉ።  መኳንንቱም እየቀረበ  መስቀል እየተሳለመ  ወደ ጦር ግንባር ሄደ።

11:30 (5:30 am)        

የሸዋ ፈረሰኛ ጦር ወደ ንጉሠ ነገሥቱ መጥቶ፣ የፈረንጅ ጦር፣ አባ ገሪማ፣ ላይ መታየቱን አስታወቀ። ከዚያም ዐጤ ምኒልክ፣ እቴጌ ጣይቱ እና ፈረሰኛው ጦር ወደ አባ ገሪማ ሄዱ።

12:00 (6:00 am)        

የዐጤ ምኒልክ ቃፊሮች(ወታደሮች)፣የጠላትን  እንቅስቃሴ በየአቅጣጫው እየተከታተሉ ለዐጤ ምኒልክ እያሳወቁ፣  ቦታቸው ላይ በተጠንቀቅ ሆነው የጠላትን ጦር ይጠብቁ ነበር።

አልቤርቶኒም 4500 ጦሩን እየመራ  ከንጋቱ 12 ሰዓት ላይ ኪዳነ ምሕረት ደረሰ።

12:10 (6:10 am)        

አልቤርቶኒ ከሚመራው ጦር፣  የተወሰነው አቅጣጫውን ለውጦ ሲጓዝ፣  በቀጥታ በንጉሥ ተ/ሃይማኖት  የሚመራው ጦር እሰፈረበትና፣  ከባድ መሣሪያ ጠምደው እሚጠብቁበት ቦታ ገቡ። ያን ጊዜ ከባዱ ጦርነት ፈነዳ።King Tekile Haymanot                                                                     ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት

12:15 (6:15 am)     

በእሻሾ ተራራ ላይ   ተጠባባቂ ጦሩን የያዘው  ዋናው አዛዥ ጄኔራል ባራቲየሪ፣ የአልቤርቶኒ ጦር የት እንዳለ እንዲነግረው መልእክተኛ ላከ።

1:45 (7:15 am)                                                                  

ባራቲየሪ ካገኘው መረጃ በመነሳት፣  በአልቤርቶኒ እና በአሪሞንዲ ብርጌዶች መኻከል ያለው ቦታ  ሩቅ  መሆኑን ለማወቅ ቻለ። በዚህ ጊዜ ባራቲየሪም፣ ዳቦርሚዳ ወደ   ግራ  ታጥፎ፣  መኻል ያላውን ጦር በስተግራው ሆኖ  እንዲረዳው አዘዘ። ይሁን እንጂ፣ ዳቦርሚዳ ባልታወቀ ምክንያት፣  የታዘዘውን ትቶ  ፣ በተቃራኒው ወደ   ቀኝ  ታጥፎ ወደ   ማርያም ሸዊቶ በማቅናት፣  ከሌላው ተለይቶ በጣም ርቆ  ሄደ። (ምናልባት  መልእክተኛው የንጉሡ ድርብ   ሰላይ  ይሆን?)

በዚህ ጊዜ፣  የራስ መኮንንና የራስ አሉላ ጥምር ጦር፣  አጋጣሚውን በመጠቀም፣ ይህን ተነጥሎ ለብቻው የመጣውን ጦር፣  በገላጣው ሜዳ  ላይ ሊወጋው ወጣ።  ከንጉሥ ተ/ሃይማኖት  ሠራዊት ጋር  ጦርነት የገጠመው አልቤርቶኒ፣  ጠንክሮ መዋጋቱን ያዩት እቴጌ ጣይቱና ራስ  መንገሻ፣ ዐጤ ምኒልክን፣  ምርጥና ጠንካራ የሆነውን 25 ሺህ  የቤተ መንግሥቱን ጦር እንዲልኩና ኢጣሊያኖቹን እንዲወጉ አሳሰብዋቸው።

2:15 (8:15 am)       

አልቤርቶኒ በአስቸኳይ ተጨማሪ ጦር እንዲላክለት፣ መልእክተኛ ወደ ባራቲየሪ ላከ።

2:30 (8:30 am)    

በዐጤ ምኒልክ 25 ሺህ  ጦር ላይ፣  እቴጌ ጣይቱ 3  ሺህ  ተጨምሮበት በድምሩ 28ሺህ፣  አልቤርቶኒን እንዲያጠቃ ተላከ።

3:00 (9:00 am)          

የቤተ መንግሥቱ ምርጥ ወታደሮች፣  ከመላው የኢትዮጵያ  ሠራዊት በጀግንነት የታወቁና የተፈሩ  ነበሩ። አልቤርቶኒን ማጥቃት በጀመሩ በግማሽ ሰዓት   ውስጥ፣ ምሽጉን ሰብረው ገብተው፣  ጄኔራሉን ራሱን ማረኩት። የተረፈውም ጦር ወደ ኋላ እግሬ አውጭኝ ብሎ ሸመጠጠ። 2  ማይልስ ላይ ርቀት ላይ እየተዋጋ ወዳለው ወደ  አሪሞንዲ ተፈተለከ።

አሪሞንዲ ጠንክሮ በውጊያ ላይ   እያለ፣ ከተደመሰሰው የአልቤርቶኒ ጦር ተርፈው የሚሸሹትን ወታደሮች የሚከታተለው የዐጤ ምኒልክ ምርጥ ጦር ደርሶ ማጥቃት ሲጀምር፤  አሪሞንዲ ሊቋቋመው አልቻለም።

3:15 (9:15 am)          

እንደ ማዕበል እየጐረፈ የመጣው የኢትዮጵያ ጦር፣ በመጨረሻ የአርሞንዲን የሰፈረበት ቦታ ላይ ወጥቶ በጨበጣ ውጊያ ተያያዘው።

ባራቲየሪ ተጠባባቂ ጦሩን ይዞ ወደ   ጦርነቱ ቦታ  ሲደርስ፣  ከአሪሞንዲ በስተቀረ ሌላ  የሚዋጋ ጦር አልነበረም። በርቀት የአልቤርቶኒ ወታደሮች ሬሳ  ምድሩንሞልቶታል። እንዲሁም ቅጥረኛ ወታደሮቹ ወደ ታች ሲሮጡ ተመለከተ። ዳቦርሚዳ ግን  የት እንደገባ ማወቅ አልቻለም።

4:00 (10:00 am)        

የራስ መንገሻና የራስ ሚካኤል ጦር፣  ከሌላ አቅጣጫ ሆኖ፣  የአርሞንዲን ጦር ማጥቃት ጀመረ። ብዙም ሳይቆይ የአርሞንዲ  ወታደሮች ከነመሪያቸው ጭምር ተገደሉ። በስተግራም በኩል፣  ኮሎኔል ጋሊያኖ የሚመራው ጦር፣  የዐጤ ምኒልክ ልዩ  ጦር ከደረሰበት በኋላ፣  በትንሽ ደቂቃ   ውስጥ ብትንትኑ ወጣ። ጋሊያኖም ከነወታደሩ እንዳለ የውሃ ሽታ  ሆኖ  ቀረ፤ ለወሬ   ነጋሪ   እንኳ የተረፈ ሰው  አልነበረም።

5:30 (11:30 am)       

ባራቲየሪ ይዟቸው የመጣው ተጠባባቂ ብርጌዶች፣  ከጀግኖቹ ኢትዮጵያውያን ጋር ጦርነቱን ቀጠሉ። ይሁን እንጂ፣  ቆራጦቹን የኢትዮጵያ ጀግኖች መቋቋም አልቻለም፤ ብዙ  ኢጣሊያኖች ክፉኛ   እየተመቱ መውደቅ ጀመሩ። ባራቲየሪም ሽንፈቱን ስላወቀ፣  የቀረውን ወታደር ማስጨረስ አልፈለገም።  የተረፈውን ጦር ይዞ ወደ   አዲግራት ፈረጠጠ።  አንዳንዶቹማ ጠረፍ እስኪደርሱ ድረስ ለዐፍታ እንኳ አልቆሙም ነበር።Ras Mekonnen

ራስ  መኮንን

8:00 (2:00 pm)       

በዚህ ጊዜ የዳቦርሚዳ ጦር ማርያም ሸዊቶ ላይ፣  ባለፈው 4  ሰዓት፣ ከኢትዮጵያ  ሠራዊት ጋር  በጦርነት እንደተጠመደ ነው። እስካሁን ከባራቲየሪ ምንም  ነገር ስላልሰማ፣ተጨማሪም ጦር ስላልመጣለት፣  ከፍተኛ ችግር መፈጠሩን ተገነዘበ። ስለዚህ፣ ቀስ  በቀስ   እየተዋጋ ወደ   ሰሜን   ለማፈግፈግ ወሰነ።

9:00 (3:00 pm)          

ይህ ሁሉ ሲሆን ጠቅላላ የጦርነቱን ዜና ዐጤ ምኒልክ ይደርሳቸዋል። ዐጤ ምኒልክ፣ ሌሎቹ ብርጌዶች ድምጥማጣቸው መጥፋቱን እንዳወቁ፣  መጨረሻ ላይ ብቻውን የቀረውን የዳቦርሚዳ ጦር፣  አንድም እንዳያመልጥ፣  የራስ ሚካኤልና በግራ ክንፍ በኩል የሚዋጋው 20 ሺህ ጦርና 8ሺህ ፈረሰኛ ወደዚያ  ሄዶ እንዲወጋ አዘዙ።

ዳቦርሚዳም ጦሩን ይዞ በጠባቡ ሸለቆ ውስጥ ማፈግፈግ ሲጀምር፤  ፈረሰኛው ጦር ደርሶ እያራወጠ ይወጋው ጀመር። ግማሽ ሰዓት ባላሞላ ጊዜ ውስጥ ዳቦርሚዳም ከ4500  ጦሩ ጋራ  በዚያ ቦታ  ወደቁ። እስከ ምሽቱም ድረስ የቀሩትን የኢጣሊያ ወታደሮች እያሳደዱ፣  እየገደሉና እየማረኩ ቆዩ። ሲመሻሽም ፣ዐጤ  ምኒልክ ከአምባ ገሪማ ወደ   አድዋ ተመለሱ። ከዚያ ሰዓት   ጀምሮ ውጊያ እንዲቆም፤  ጠላትንም መማረክ እንጂ እንዳይገደል ሲሉ  አዘዙ።  Dejazmach Balcha Aba Nefso                                                            ደጃዝማች ባልቻ  አባ ነፍሶ

ከጥቂት ጊዜ በኋላ ሽለላ፣ ፉከራ፣ የድል ዘፈን፣ እልልታ ማስተጋባት ጀመረ።  ዐጤ   ምኒልክም፣ በዛሬው ቀን  በዚህ ጦር ሜዳ   ተዋግተው የወደቁት ክርስቲያኖች ናቸውና፤  ዘፈኑ ሆነ  ሽለላውን ወዲያው እንዲቆም አዘዙ። ዐጤ   ምኒልክም፣  ለክብራቸው ተዘርግቶ የነበውን ቀይ  ዣንጥላ ታጥፎ በምትኩ ጥቁር ዣንጥላ እንዲዘረጋ አዘዙ።  ከባድ ዝናብም ጣለ። እቴጌም ለሀገራቸው ክብር የወደቁትን ጀግኖች ስም   ሲነገራቸው እንባቸውን ያፈሱ ነበር። ምንም እንኳ ጦርነቱ በኢትዮጵያውያን ድል አድራጊነት ቢጠናቀቅም፤  መኳንንቱና ሠራዊቱ በዚያች ቀን  ጀንበር ሳትጠልቅ በጦርነቱ ላይ የወደቁትን፣ በሺህ   የሚቆጠሩ ወገኖቻቸውን እያሰቡ  በኀዘን ተውጠው ነበር።

የአድዋ  ጦርነት በታላቁ ዐጤ   ምኒልክ መሪነት፣  ኢትዮጵያውያኑ አንድ የሰለጠነን የአውሮጳ ጦርበማሸነፍ ተጠናቀቀ። በዚህ ጦርነት 13,300  ኢጣሊያኖች ሲሞቱ 700   ተማርከዋል። ከእነዚህም ውስጥ ጦርነቱን የመሩት 2  ጄኔራሎች አሪሞንዲና ዳቦርሚዳ ሲገደሉ፤  ጄኔራል አልቤርቶኒ ደግሞ ተማርኳል። በኢትዮጵያውያን በኩል   20,000  ሲወድቁ ፣ 7000 ደግሞ ቆስለዋል።

Leave a comment

This site uses Akismet to reduce spam. Learn how your comment data is processed.

Start a Blog at WordPress.com.

Up ↑